ከሞት የበለጠ ኃይል

Samir From Iraqi

ትርጉምና ቅንብር በአዘጋጁ

የተወለድኩት የሙስሊም እምነት አጥባቂ ከሆኑ የኢራቅ ቤተሰብ ውስጥ ነው፡፡ በመካከለኛው የትምህርት ዘመኔ ውስጥ አስተማሪዬ እስልምና በመሐመድና ከእሱ ቀጥለው ስልጣን በያዙት ተከታዮቹ እንዴት በጦርነት እንደተስፋፋ በሚገልጥበት ጊዜ ሁሉ በጣም እረበሽ ነበር፡፡ በሙስሊሞች ፀሎት ላይ እንኳን ለእግዚአብሔር ጥያቄ የሚቀርበው ሁኔታቸውንና ባሕርያቸውን እንዲለውጠው ሳይሆን የአካባቢያቸው ሁኔታ ብቻ እንዲለወጥ ነው፡፡ ስለዚህም አስተማሪዬ ስለ እስላሞች ጀብዱና የጦርነት ጀግንነት ሲናገር እኔ በውስጣቸው እመለከት የነበረው እስልምና ጥላቻን፣ ስግብግብነትን ግድያንና ስርቆትን እንዳስፋፋ እና ለማስፋፋትም እንደሚያበረታታ የጦርነት ወንጀል አድርጌ ነበር፡፡

ዓመታትም እየጨመሩ በመሄዳቸው የመካከለኛ ትምህርቴን አጠናቀቅሁና ወደ ውትድርና እንድቀላቀል ተገደድኩኝ፡፡ በተቀላቀልኩትም በጦሩ ውስጥ እኔ የጦር ታንክ ሾፌር ሆንኩኝ፡፡ ሆኖም በ1980ዎቹ በሆነው የኢራንና የኢራቅ ጦርነት ወቅት እኔ በጦርነቱ አልሳተፍም አልኩኝ፡፡ ስለዚህም ወደ ሞትና ወደ ጥፋት ከሚወስደው መንገድ ይልቅ የሰላምንና የፍቅርን መንገድ መረጥኩኝ፡፡ ምርጫዬም አደገኛ ውጤትን እንደሚያስከትልም አስተዋልኩኝ ማለትም እስራትን ቶርቸርን ምናልባትም ሞትንም እንደሚያስከትል ተረዳሁኝ፡፡

ከጦሩም ለማምለጥ ወሰንኩኝ፡፡ ከጓደኞቼም መካከል ከእኔ ጋር አብሮ ሊሄድ የሚችል እንዳለ ስጠይቅ ማንም ፈቃደኛ ስላላገኘሁ ብቻዬን በከፍተኛ ጦርነትና አደገኛ በሆኑ የተቀበሩ ፈንጂዎች መካከል አልፌ ኤል ሞሱል በሚገኘው ቤቴ በተዓምራት ደረስኩኝ፡፡ እቤትም እንደደረስኩኝ ቤተሰቦቼ አንቀበልህም ሲሉኝ እንዲያውም እቤትም እንኳን እንድቆይ አንፈቅድም ሲሉኝ በጣም ተደናገጥኩኝ፡፡ እነሱም በጦርነቱ መሳተፌን እንድቀጥል ወደ ግንባር ተመልሼ እንድሄድ ሊያስገድዱኝ ሞከሩ፡፡ ስለዚህም አገሩን ጥዬ ወደ ሶርያ ለመሄድ ወሰንኩኝ፡፡

ወደ ሶርያ ቦርደር ለማለፍ ስሞክር የኢራቅ ጦር ሰላዮች በሆኑ በሁለት ዘላኖች ተያዝኩኝ፡፡ እነሱም በአቅራቢያ ላለው ለኢራቅ ጦር ሠራዊት አሳልፈው ሰጡኝ፡፡ በጣም በቶርች ተደብድቤ እና ልገደል ተወስኖ ዓይኖቼ ታስረው የምገደልበትን ቀናቶች መጠባበቅ ጀመርኩኝ፡፡ ነገር ግን ሐሳባቸውን ቀይረው ወደ ባግዳድ እንድሄድና በማዕከላዊው ስለላ አገልግሎት ስር በታላቅ አገር መክዳት ወንጀል (ምክንያቱም በጦርነት ወቅት ከወታደራዊ አገልግሎት ታላቅ የአገር መክዳት በሞት ፍርድ የሚያስቀጣ ታላቅ ወንጀል ነውና) እንድከሰስ ተደረገ፡፡

በጦር ሰራዊት የሰው እስር ቤት ውስጥም ፍርድን በመጠባበቅ ለ16 ወራቶች ቆየሁኝ፣ ከዚያም ፍርድ ቤት በቀረብኩበት ጊዜም የከሳሽ ምስክሮች የነበሩት ሁለቱ የያዙኝ ዘላኖች ነበሩ፡፡ በዚህም አስቸጋሪ ወቅት ከዚህ እጅግ አደገኛ ከሆነው ሁኔታ ውስጥ እግዚአብሔር እንዲያወጣኝ ፀለይኩኝ፡፡ በሚያስደንቅም ሁኔታ በቂ ማስረጃ የለም ብሎ ፍርድ ቤቱ በነፃ ለቀቀኝ ምክንያቱም አንደኛው ምስክር እውርና ድዳ ስለነበረ እና በፍርድ ቤት ሊመሰክር ስላልቻለም ጭምር ነበር፡፡ በዚህ ወቅት እግዚአብሔር እኔን  ስላዳነኝ ጥልቅ የሆነ የእግዚአብሔርን ፍቅር ተሰማኝ፡፡ ከዚያም በእሱ ላይ ይበልጥ መተማመን አደረብኝ፡፡

ቆይቶም ወደ ቀጠለው ጦርነት እንድሄድና ተመልሼም በውጊያው ላይ እንድሳተፍ ተገደድኩኝ በመሆኑም እራሴን እንደገና ታንክ ስነዳ አገኘሁት፡፡ ያለፈው የማምለጥ ልምዴ እንዳለ ሆኖ አሁንም ለማምለጥ ወሰንኩኝ፡፡ በዚህ በሁለተኛው ማምለጥ ወደ በኢራን ድንበር ወዳለችው ወደ ኩርዲሲታኒ ከተማ ሄድኩኝ፡፡

እኔም 400 ማይልስ ያህል በማዕድን ሜዳዎችና በእግሬ እየሄድኩና ተራራዎችን እያቋረጥሁ ድንበሩ እስከምደርስ ድረስ ተጓዝኩኝ፡፡ እዚያም እስር ቤት በመሰለ የስደተኞች ካምፕ ውስጥ ታስሬ እያለሁ እኔና ሌሎቹ እስረኞች የእስልምናን ትምህርት ለመለማመድ እንገደድ ነበር፡፡ ስለዚህም አሁንም እንደገና ከዚህ ለማምለጥ ወሰንኩኝ፣ በዚህ ጊዜ ወደ ፓኪስታን ለሦስት ቀናትና ለሦስት ሌሊቶች ያለምንም ምግብና ያለምንም ውሃ የሞትኩ እስክመስል ድረስ መጓዝ ነበረብኝ፡፡

በፓኪስታን ውስጥ ለአንድ ዓመት ያህል ቤት የለሽ ሆኜ ቆየሁኝ፣ ከዚያም ወደ ሕንድ ለማቋረጥ ወሰንኩኝ፡፡ ይህንንም ስወስን በፓኪስታንና በሕንድ መካካል ከነበረው የድንበር የጦርነት ውጥረት ከፍተኛ አደጋ ባሻገር ነበር፡፡ አሁንም አንድ ጊዜ እንደገና እግዚአብሔር ሕይወቴን በተዓምራቱ ከአደጋ አዳናት፡፡ በእነዚህ ጊዜያት ሁሉ ውስጥ እግዚአብሔር አጠገቤ እንዳለና ከማንኛውም አደጋ ሁሉ እንደሚጠብቀኝ ሆኖ ይሰማኝ ነበር ይህም በመጨረሻ ምን መልካም ነገር ለእኔ እንዳዘጋጀልኝ እንኳን ምንም የማውቀው ነገር ሳይኖር ነበር፡፡

በደቡብ ቻይና አልፌ በኔፖል ዋና ከተማ ካታማንዱ ከደረስኩኝ በኋላ እግዚአብሔርም በቀጥታ በእኔ ሕይወት ውሰጥ መስራትንና መናገርን ጀመረ፡፡ ስለታመምኩኝም ወደ ሆስፒታል መሄድ ነበረብኝ፣ በሆስፒታልም ውስጥ በክርስትያኖች ኮሚቴ ውስጥ የምትሰራን አንዲት ነርስን ተገናኘሁኝ፡፡ እሷም ከዓለም ውስጥ ከተውጣጡ የሚሽነሪዎች ማህበረሰብ ጋር አስተዋወቀችኝ፡፡ እነሱም ዴላ ኤም ሃውስ በተባለ በአንድ ቦታ ላይ አብረው ይኖሩ ነበር፡፡

እነዚህ ሰዎች ወደዚህ ቦታ የመጡት ክርስቶስን ለማገልገል በሚል ብቸኛ ዓላማ ነበር፡፡ እነሱም የክርስቶስን ወንጌልን ለመስበክ ወደ እስር ቤቶች ሆስፒታሎች እና ወደ ድሃዎች አካባቢዎች ይሄዱ ነበር፡፡ እኔም ወደ እነሱ መኖሪያ ቤት እንድሄድ ተጋበዝኩኝና ምንም ሳላመነታ ሄድኩኝ፡፡ እዚያም ሄጄ ያየሁት ነገር በጣም በፍቅር የተሞሉ፣ ርህራሄ ያላቸው እና ሕይወቱን ለሰዎች ሁሉ በሰጠው በክርስቶስ ኢየሱስ ስም ድሃዎችን ሁሉ ለመርዳት ትልቅ መሻት የነበራቸው ሰዎችን ነበር፡፡

በእነሱም ቤት ውስጥ ጥራት ያለውን የህክምና አገልግሎትን በተገኘው ተረኛ አማካኝነት እያገኘሁ ለሠላሳ ቀናት ያህል ቆየሁኝ፡፡ በሕይወቴ ሁሉ ካየሁት እጅግ በጣም ጥሩው ጊዜ የዚያን ጊዜ ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ስለጠበቀኝ ስለ አፍቃሪው አምላክ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ተማርኩኝ፡፡ በየጠዋቱ ሁላችንም በቁርስ ጠረጴዛ ዙሪያ እንሰበሰብና ምስጋናዎችን በመዘመርና መጽሐፍ ቅዱስን እናጠና ነበር፡፡ ጌታ ኢየሱስም እራሱ በመካከላችን እንዳለ ሆኖ ነበር የሚሰማኝ፡፡ ከዚያም ስብሰባ በኋላ እያንዳንዱ ሚሽነሪ ወደ ዕለት አገልግሎቱ ይሄድ ነበር፡፡  

እዚያም ስለ ኢየሱስ ብዙ ነገሮችን ተማርኩኝ ለሌሎች ሰዎችም መፀለይን እንዲሁም ከምግብ በፊት መፀለይንና ስለ አባታችን ሆይ ፀሎት ሁሉ ተማርኩኝ፡፡ እነሱም ስለ ጌታ ኢየሱስ የማዳን ሞት ነገሩኝ፡፡ በእነዚህም ሕዝቦች በጣም መወደዴ ልዩ ስሜትን ፈጠረብኝ ምክንያቱም በጥላቻ ስሰደድና ሰላምን ስፈልግ ነበርና፡፡ እነሱም ከእነሱ ጋር እንድቆይ በመደጋገም ቢጠይቁኝም እንኳን መጥፎ ምርጫን በማድረግ የግል ነፃነት የተባለውን የጣረሞት ሕልሜን ለማግኘት ከእነሱ ተለይቼ መሄድን መረጥሁ፡፡

ስለዚህም ከእነሱ ርቄ ወደ ታይላንድ ሄድኩኝ እዚያም እራሴን ያገኘሁት በከተማዎችና በወደቦች መካከል በመንከራተት እየደከምኩ ነበር፡፡ የሞት ግድያም ተስፋፍቶበት ወደነበረበት ወደ ትውልድ ከተማዬ ለመመለስ እስክወስን ድረስ እጅግ በጣም ተስፋ ቆረጥኩኝ፡፡ ወደ ትውልድ ከተማዬ ስመለስም በእኔ ላይ ስለሚሆነው ምንም ነገር ግድ አልነበረኝም ምክንያቱም በኢየሱስ ፍቅር ተማምኜ ነበርና፡፡ ልክ እንደደረስኩም በኢራቅ የስለላ አገልግሎት ተይዤ ምርመራ ተደርጎልኝ ተገርፌ ታሰርኩኝ፡፡ ቀጥሎም በሐሰት ተከስሼ ወደ ፍርድ ቤት ተወሰድኩኝ እነሱም ወንጀለኛ ሊያደርጉኝና ሊያስገድሉኝ ብዙ ተስፋ አድርገው ነበር፡፡

ጌታ ለእኔ ባለው ፍቅርና ጥበቃም ሙሉ ለሙሉ በመተማመን ወደ ፍርድቤት ሄድኩኝ፡፡ ፍርድ ቤቱም እኔ ከምገደል ይልቅ ለሃያ ዓመታት እንድታሰር ፈረደ፡፡ እኔም እንደማይገድሉኝ በማወቄ እጅግ በጣም በደስታ ተሞልቼ በጣምም ተደነቅሁ፡፡ እንደ ፖለቲካም እስረኛ ወደ ማዕከላዊው እስር ቤት ተወሰድኩኝ፡፡ እዚያም ለአንድ ዓመት እንደታሰርኩኝ የኢራቅ መንግስት የፖለቲካ እስረኞችን በሙሉ ለመፍታት ስለተገደደ ከእስር ነፃ ወጣሁኝ፡፡

እንደተፈታሁም ወዲያውኑ የክርስቶስን ፍቅር ለመጀመሪያ ጊዜ ወዳየሁበት በካታማንዱ ወዳለው የሚሽነሪ ቤት ለመመለስ ወሰንኩኝ፡፡ ነገር ግን ልክ ይህንን እንዳቀድሁ የኢራቅ መንግስት ኩዌትን ወረረ እኔም እንደገና ጦሩን እንድቀላቀል ተገደድኩኝ፡፡ አንድ ጊዜ እንደገና ከጦር ግንባር አምልጬ ወደ ሳዑዲ አረቢያ ድንበር የአሜሪካን ጦር ወደ ሠፈረበት አቅጣጫ ሄድኩኝ፡፡ ነገር ግን የሳዑዲ ሠራዊት ያዘኝና እንደገና ለ18 ወራት እንሰሳ እንኳን በማይኖርበት የበረሃ ዋሻ ውስጥ ታስሬ ቆየሁኝ፡፡ ይህንም እጅግ በጣም ከባድ ጊዜ እስክለቀቅ ድረስ ጌታ እያበረታኝ በእሱ ብርታት ተወጣሁት፡፡ ከዚያም ወደ አሜሪካን አገር በማምለጥ ከክርስቶስ ጋር እንድራመድ ከረዱኝ ከኢቫንጀሊካል ክርስትያን ወገኖቼ ጋር ልቀላቀል ቻልኩኝ፡፡

እኔም ከጨለማው ሕይወት ውስጥ አውጥቶኝ ወደ ወንጌል ብርሃን የመራኝን እና ምንጊዜም የማይረሳኝን ጌታዬን ሁልጊዜ አመሰግነዋለሁኝ፡፡

ለእግዚአብሔር ከዘላለም እስከዘላለም ክብር ይሁን አሜን

 

የትርጉም ምንጭ: Mightier than death 

ለእስልምና መልስ አማርኛ  ዋናው ገጽ